Saturday, October 5, 2013

ምዕራፍ ፰



፩ በእጃቸው እንዳትወድቅ ከታላላቆች ሰዎች ጋር አትከራከር፡፡

፪ በብልጽግናው ድል እንዳያደርግህ ከባለጸጋ ጋር አትጣላ፥ ብዙዎች ስለ ወርቅ ጠፍተዋልና፤ የነገሥታትም ልቡና ድል ሆኖአልና፡፡

፫ ከተናጋሪ ሰውም ጋር አትከራከር፤ ያለዚያ በእሳት ላይ እንጨት መጨመርህ ነው፡፡

፬ እናትና አባትህን እንዳታዋርድ፥ከአላዋቂ ሰው ጋር አትሣቅ፡፡

፭ ከኀጢአት የተመለሰውን ሰው አትንቀፈው፤እኛ ሁላችንም ኀጢአተኞች እንደሆን ዐስብ፡፡ 
 
፮ በርጅናው ጊዜ ሰውን አታቅልለው፥ ከእኛ የማያረጅ የለምና፡፡ 

፯ በሞተ ሰው ደስ አይበልህ፤ሁላችንም እንደምንሞት ዐስብ፡፡

፰ የብልሆች ነገር አታቃልል፤ጥበብን በእነርሱ ዘንድ ታገኛለህና፥ ምሳሌያቸውን ተማር፡፡መምህራንንም አገልግል፡፡

፱ የሽማግሎችን ምክራቸውን ጠብቅ፤ እነርሱ ከአባቶቻቸው ተአምረዋልና አንተም ከእነርሱ ተማር በኀዘንም ጊዜ የምትናገረውን ታገኛለህ የምትመልሰውንም ታውቃለህ፡፡

፲ በእሳታቸው እንዳትቃጠል፥ የኀጢአተኞች ሰዎችን እሳት አትጫር፡፡ 

፲፩ በአንደበቱ ነገር እንዳያስትህ፥ በተሳዳቢና በጠላት ዘንድ አትከራከር፡፡

፲፪ ከአንተ ለሚበለጽገው አታበድረው፤ ብታበድረው ግን ገንዘብህን እንዳጣህ ዕወቅ፡፡ 

፲፫ ከአንተ ለሚበረታውም አትዋሰው፤ብትዋሰው ግን አንተ ራስህ እንደምትከፍል ዐስብ፡፡

፲፬ ከዳኛ ጋር አትከራከር፥ እንደ ክብሩ መጠን ፍርድን ይለውጡለታልና፤

፲፭ እንዳይደፍርህ ከደፋር ሰው ጋራ መንገድን አትሂድ፤
 እርሱ ልቡ እንደ ወደደ ያደርጋልና አንተም በእርሱ ስንፍና ትሞታለህ፡፡

፲፮ ከቊጡ ሰው ጋር አትከራከር፤ በእርሱ ዘንድ ደም ማፍሰስ እንደ ኢምንት ነውና፥ ረዳት ወደሌለበት ቦታም ይወስድሃልና ከእርሱ ጋር ወደ ምድረ በዳ አትውጣ፡፡

፲፯ የሰማውን ነገር መጠበቅ አይችልምና፥ ከአላዋቂ ሰው ጋር አትማከር፡፡

፲፰ እንዴት እንደሚደርስብህ አታውቅምና፥ ጉዳይህን በባዕድ ፊት አትናገር፡፡

፲፱ ዋጋህ እንዳይጠፋብህ፥ ለሰው ሁሉ የልብህን ምሥጢር አትግለጥ፡፡