Saturday, October 5, 2013

ምዕራፍ ፯




፩ ክፋትን አትሥራት፤ ክፉም አያገኝህም፡፡

፪ ከበደል ራቅ፣ እርሷም ራስዋ ካንተ ትርቃለች፡፡

፫ ሰባት እጥፍ አድርገህ እንዳትሰበስባት፣ በኀጢአት ትልም አትዝራ፡፡

፬ ከእግዚአብሔር መንግሥትን አትለምን፤  ከንጉሥም የክብር ዙፋን አትለምን፡፡ 

፭ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቅ ነኝ አትበል፤ በንጉሥም ዘንድ ብልህ ነኝ አትበል፡፡

፮ ዳኛ መሆንን አትውደድ፤እነሆ፥ በደለኛውን ለመበቀል አትችልም ይሆናል፤እነሆ፥ ለባለጸጋም ታደላ ይሆናል በእውነት ሥራህም ላይ ኀጢአት ትሠራለህ፡፡

፯ ያገርህንም ሰው አትበድል፤ራስህንም በወገኖችህ መካከል አታስት፡፡

፰ በአንዲቱም ቢሆን ከቅጣት አታመልጥምና፣ሁለት ኀጢአት አንድ አድርገህ አትሥራ፡፡

፱ በመባዬ ብዛት እግዚአብሔር ኀጢአቴን ያስተሠርይልኛል፤ ለልዑል እግዚአብሔርም መባእ ከአገባሁ ይቅር ይለኛል አትበል፡፡

፲ በምትጸልይበት ጊዜ አትቸኩል፣ምጽዋት መመጽወትንም አታቃልል፡፡

፲፩ የሚያሳዝን፥ ደስ የሚያሰኝም አለና፣ባዘነ ሰው አትሳቅ፡፡

፲፪ በባልንጀራህ ሐሰትን ተግባር አታድርግ፤በወዳጅህና በባልንጀራህም ላይ እንዲህ አታድርግ፡፡

፲፫ በምንም ሁልጊዜ ሐሰትን አትውደድ፤ፍጻሜዋ ይጐዳሃልና፡፡

፲፬ በሽማግሌዎች መካከል ብዙ ቃል አትናገር፤በአፍህ የተናገርኸውን ስእለትህን አትመልስ፥ ቃልህንም አትለውጥ፡፡

፲፭ የእጅህንም ሥራ አታቃልል፥ፈጣሪህም የሚያበቅልልህን ቡቃያህን ቸል አትበል፡፡

፲፮ ብዙ ናቸው ብለህ ከኀጢአተኞች ጋር አንድ አትሁን፡፡

፲፯ ጥፋት እንደማትዘገይ ዐስብ፥ሰውነትህን ፈጽመህ አዋርዳት፥የኀጢአተኞች ፍዳቸው ትልና እሳት ነውና፡፡

፲፰ በእየነጋው ወዳጅ አትለውጥ፤ ስለ ቀይ ወርቅ ወዳጅህን አትጣ፡፡

፲፱ መውደዷ ከወርቅ ይወደዳልና ብልህና ደግ ሴትን አትጥላ፡፡

፳ በእውነት በሚገዛልህ ቤተሰብህ ላይ፥  ስለ አንተ ሰውነቱን አሳልፎ በሚሰጥ በምንደኛህም ላይ ክፉ ነገርን አታድርግ፡፡

፳፩ ብልህ ቤተ ሰብህን እንደ ራስህ ውደደው፤ ነጻ ታወጣውም ዘንድ ተስፋ ያደረገህን ዋጋውን አታጥፋበት፡፡

፳፪ ሁልጊዜ ከብትህን መፍቀድ አትተው፤ ከእነርሱ የሚጠቅምህን ወደ አንተ አቅርብ፡፡

፳፫ ልጆች ቢኖሩህ ምከራቸው፤ከሕፃንነታቸው ጀምረህ ትሕትናን አስተምራቸው፡፡

፳፬ ሴቶች ልጆችም ቢኖሩህ ጠብቃቸው፤አታስታቸው፥ አትሣቅላቸው፥ አታባብላቸውም፡፡

፳፭ ልጅህን አቅመ ሔዋን ስታደርስ አጋባት፥ጠብቃት፥ ታላቅ ሥራንም ትፈጽማለህ፥ ከድካምም ታርፋለህ፥ነገር ግን ለብልህ ሰው አጋባት፡፡

፳፮ እንደ ራስህ የምትወዳት ሚስት ብትኖርህ አትፋታት፡፡

፳፯ በፍጹም ልቡናህ አባትህን አክብረው፥የእናትህንም ምጧን አትዘንጋ፡፡

፳፰ በእነርሱም ምክንያት እንደ ተወለድህ ዐስብ፤ስላደረጉልህስ ፋንታ ምን ታደርግላቸዋለህ?

፳፱ በፍጹም ሰውነትህ እግዚአብሔርን ፍራው፤ካህናቱንም አክብራቸው፡፡

፴ በፍጹም ኀይልህም ፈጣሪህን ውደደው የሚያገለግሉትንም አትተዋቸው፡፡

፴፩ እግዚአብሔርን ፍራው፤ የሚያገለግለውን ካህኑንም አክብረው፤ የታዘዘልህ ዕድሉንም ስጠው፤ቀዳምያቱንና፥ ስለ ኀጢአት የሚሠዋውን መሥዋዕት፥ወርቹንም፥ ማታና ጧትም የሚሠዋውን መሥዋዕት፥መጀመርያ የሚወለደውንም ከብት ስጠው፡፡

፴፪ በረከትህ ፍጽምት ትሆን ዘንድ እጅህን ለድሃ ዘርጋ፡፡

፴፫ ስጦታ በሕያው ሁሉ ፊት ጸጋ አለው፥ ስለ ሞተ ሰውም ምጽዋት መስጠትን አትተው፡፡

፴፬ ከሚያለቅሱ ሰዎችም አትለይ፥ከሚያለቅሱም ጋር አልቅስ፡፡

፴፭ ሕመምተኛንም ሰው መጐብኘት ቸል አትበል በዚህም ይወዱሃል፡፡

፴፮ በተናገርኸው ነገር ሁሉ ፍጻሜህን ዐስባት፥ ሁልጊዜም አትበድል፡፡