፩ ጠላት
ከምትሆን ወዳጅ ሁን፤ የክፉ ስም ፍጻሜው ስድብና ውርደት ነውና፤ ምላሱ ሁለት የሆነ ኀጢአተኛ ሰውም እንዲህ ነው፡፡
፪ ከልቡናህ
ባነቃኸውም ምክር ራስህን ከፍ ከፍ አታድርግ፤ አንበሳ ላምን እንደሚነጣጠቅ ሰውነትህን እንዳይነጥቋት፡፡
፫ ቅጠልህን
ይበላብሃል፥ ፍሬህንም ታጣለህ፤ እንደ ደረቅ እንጨትም ይጥልሃል፡፡
፬ ክፉ ሰውነት
ገንዘብ ያደረጋትን ሰው ታጠፋዋለች፤ ጠላቱንም በእርሱ የጨከነ ታደርገዋለች፡፡ እውነተኛና እውነተኛ ያልሆነ ጓደኝነት
፭ ልዝብ
አንደበት ወንድማማችነትን ያበዛል፤ ልዝብ አፍም ወዳጅን ያበዛል፡፡
፮ ብዙ ሰዎች
ወዳጆች ይኑርህ፤ነገር ግን ከብዙዎቹ አንዱ ምክርህን የምትገልጥለት ይሁን፡፡
፯ ወዳጅ
ብታበጅ ነችግርህ ወራት ወዳጅ አብጅ ፈጥነህም እምነት አትጣልበት፤
፰ ለጥቂት ቀን
የሚሆን ወረተኛ ወዳጅ አለና በመከራህም ጊዜ ከአንተ ጋር አይታገሥም፡፡
፱ ጠላት
የሚሆንህና፥ የሚሰድብህ፥ ሰውረህ የሠራኸውን ኀጢአትህንም የሚገልጥብህ ወዳጅ አለ፡፡
፲ ስለ
ማዕድህም የሚወድህ ወዳጅ አለ፤ እርሱም ከአንተ ጋራ አይኖርም፥ በተቸገርህም ጊዜ ይለይሃል፡፡
፲፩ ባለጸጋ
በሆንህ ጊዜ እንዳንተ ይሆናል፤ ቤተ ሰብህንም ይገዛል፡፡
፲፪ ብትቸገር
ግን እርሱ ባለጋራህ ይሆናል፤ እንዳታየውም ይሰወርሃል፡፡
፲፫ ከጠላቶችህ
ራቅ፥ ወዳጆችህንም ተጠባበቃቸው፡፡
፲፬ የታመነ
ወዳጅ እንደ ጸና አላባሽ አግሬ ጋሻ ነው፤እርሱን ያገኘ ሰው ድልብ አገኘ፡፡
፲፭ ለታመነ
ወዳጅ ለውጥ የለውም፤ለደግነቱም ሚዛን የለውም፡፡
፲፮ የታመነ
ወዳጅ የሕይወት መድኀኒት ነው፤እግዚአብሔርንም የሚፈሩ ያገኙታል፡፡
፲፯
እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ወዳጅነቱን ያጸናል፤ባልንጀራው እንደ እርሱ ይሆነዋልና፡፡
የጥበብ በረከት
፲፰ ልጄ ሆይ፥
በሕፃንነትህ ጥበብን ምረጣት እስክታረጅም ድረስ ታገኛታለህ፡፡
፲፱
እንደሚያርስና እንደሚዘራ ሰው ወደ እርስዋ ሂድ፤የተባረከ ፍሬዋንም ጠብቅ፤ ስለ እርስዋ በመሥራት ጥቂት ትደክማለህ፤ ነገር ግን
ፈጥነህ ፍሬዋን ትበላለህ፡፡
፳ በሰነፎች
ዘንድ ፈጽማ ጐጣጕጥ ናት፤አእምሮ በሌለው ሰውም አታድርም፡፡
፳፩ የፈተና
ድንጋይ አንሥተው በተሸከሙት ጊዜ እንዲከብድ፥እንደዚሁ ትከብደዋለች፤ፈጥኖም ይጥላታል:፡
፳፪ ጥበብስ
እንደ ስሟ ናት፤ብዙ ሰዎችም የሚያውቋት አይደሉም፡፡
፳፫ ልጄ ሆይ፥
ስማኝ፥ በምክሬም ጽና፤ምክሬንም አታቃልል፡፡
፳፬ እግሮችህን
ወደ ቀንበርዋ አግባ፤ ዛንጅርዋንም ባንገትህ እሰር፡፡
፳፭ ጫንቃህን
ዝቅ አድርገህ ተሸከማት፤በእግር ብረትዋም አትበሳጭ፡፡
፳፮ በፍጹም
ነፍስህ ወደ እርሷ ተሰማራ፤ በፍጹም ኀይልም መንገድዋን ጠብቅ፡፡
፳፯ ፍለጋዋን
ተከተል፥ ፈልጋት፥ ታገኛታለህም፡፡ያዛት፥ አትተዋትም፡፡
፳፰ በፍጻሜህም
ዕረፍትን ታገኛለህ፤ደስታም ይሆንሃል፡፡
፳፱ እግር
ብረትዋም እንደ ጽኑ ጋሻ ይሆንልሃል፤ዛንጅርዋም የክብር ልብስ ወደ መሆን ይመለስልሃል፡፡
፴ የዘለዓለም
ወርቅ በእርሷ ዘንድ አለና፤ማሰርያዋም የሰማያዊ ሐር ጌጥ ይሆንሃል፡፡
፴፩ እንደ
ክብር ልብስ ትለብሳታለህ፣ የደስታ ዘውድንም ታቀዳጅሃለች፡፡
፴፪ ልጄ ሆይ፥
ብልህ ትሆን ዘንድ ብትወድድ፣ትማርም ዘንድ በልቡናህ ብትጨክን፣
፴፫ ትሰማ
ዘንድ ብትወድም ታገሥ፤ ጆሮህንም ብታዘነብል ብልህ ትሆናለህ፡፡
፴፬ በብዙ
ሽማግሌዎች ዘንድ ቁም፤ ከእነርሱም ዐዋቂ ሰው ብታይ ተከተለው፡፡
፴፭ የመጽሐፉን
ነገር ሁሉ ፈጥነህ ስማ፤የጥበብም ምሳሌ አይዘንጋህ፡፡
፴፮ ብልህ ሰው
ብታይ ፈጥነህ ወደ እርሱ ሂድ፤እግርህም በደጃፉ መድረክ ይመላለስ፡፡
፴፯
የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ዐስብ፤ መጻሕፍቱንም ሁልጊዜ አንብብ፣ እርሱም ልቡናህን ያጸናዋል፤ጥበብንም ትወዳት ዘንድ ይሰጥሃል፡፡