Saturday, October 5, 2013

ምዕራፍ ፩

መጽሐፈ ሲራክ ኢያሱ ሲራክ የተነገረው ነገር ይህ ነው፤ኢያሱ ማለት መድኃኒት ማለት ነው፤ሲራክ ማለት ጸሐፊ ነው፤የኢየሩሳለም ሰው የአልዓዛር ልጅ እኔ ኢያሱ ሲራክ ኢታምልክን ዘጠኙን ሕግጋት በዚህ መጽሃፍ ጻፍኩ። 

የጥበብ መንገዶች

ምዕራፍ
 
፩፤ የጥበብ ሁሉ መገኛዋ ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው ዓለም ሳይፈጠር ጥበብ ከርሱጋር ነበረች።

፪፤ የብህር አሸዋን የዝናም ጠብታን የዘመንን ቁጥር ማን ቆጠረ።

፫፤ የሰማይን ምጥቀት የምድርን ስፋት የባህርን ጥልቀት ጥበብን ማን መርምሮ አወቃቸው።

፬፤ ጥበብ ከሁሉ አስቀድሞ ተፈጠረች።
 
፭፤ የጥበብ መታሰቧ ከጥንት ጀምሮ ነው።

፮፤ የጥበብ ምስጢሯ ለማን ተገለጠ።
 
፯፤ምክሯንስ ማን አወቀ።
 
፰፤ ጥበብ አንድ ነው በማያውቁት ሰዎች ዘንድ ፈጽሞ የሚያስፈራ ነው እግዚአብሔር በዙፋኑ ጸንቶ ይኖራል።
 
፱፤እርሱ እግዚአብሔር ጥበብን ሰራት አስተማራት ሰፈራትም።

፲፤ እንደ ስጦታው ሰው በስጋዊ ሰው ሁሉ አሳደሯት ለሚወዷት ሰዎችም ሁሉ ሰጣቸው።

፲፩፤እግዚአብሔርን መፍራት ክብር ነው የሚያስመካ ተድላ ደስታም ነው ፤ተድላ ደስታ ያለው ዘውድም ነው።

፲፪፤እግዚአብሔርን መፍራት የልብተድላ ደስታ ነው ተድላ ደስታን ይሰጣል፤ደስም ያሰኛል በህይወት የሚኖሩበትን ዘመን ያበዛል።

፲፫፤እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ፍጻሜው ያምራል የሚሞትበት ቀንም የከብራል።

፲፬፤ የጥበብ መጀመርያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው ከናታቸው ማህጸን ከተወለዱ በኋላ ለምዕመናን ታሰራለች።
 
፲፭፤ ከጥንት ጀምሮ ለሰው ተፈጠረች ከልጆቻቸው ጋራ ጸንታ ልትኖር ታመነች።
 
፲፮፤ጥበብን መጥገብ እግዚአብሔርን መፍራት ነው ምሥጢሩን ትገልጥላቸዋለች።
 
፲፯፤በመምህራን ጉባኤ ተድላ ደስታ መልቷል በቦታዋም ትምህርት አለ።
 
፲፰፤ የጥበብ ዘውዷ እግዚአብሔርን መፍራት ነው ፍቅር አንድነትን ያመጣታል ፈጽሞ ያድናል።

፲፱፤ጥበብን ፈጣሪዋ ሰራት ሰፈራትም ለሰውም ገለጣት የምክርንና የእውቀትን የጥበብንም ምሥጢር ገለጠየሚያጸኗትንም ሰዎች አገነናቸው አከበራቸው።
 
፳፤ የጥበብ መጀመርያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው ሥራቷም በህይወት የሚኖሩበትን ዘመን ያበዛል።

፳፩፤በተቆጣ ግዜ መከራ ይመጣበታልና ቍጡ ዓመጸኛ ሰው አይጸድቅም።
 
፳፪፤ጊዜዋን እስክታሳልፍ ድረስ ነገርህን ቍጣን ታገሳት ኋላ ደስ ታሰኝሃለች።
 
፳፫፤ጊዜውን እስክታገኝ ድረስ ነገርህን ሠውር ብዙ ሰዎች ጥበብህን ይናገራሉ።
 
፳፬፤በመምራን ጉባኤ መስለው የሚያስተምሩት ትምህርት አለ።ኃጢአተኛ ሰው እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰውን ይጸየፈዋል።

፳፭፤ጥበብን ከወደድካት ትእዛዙን ጠብቅ ጥበብም ጥበብን ይሰጥሃል።

፳፮፤ጥበብ ይሉሃል እውቀት ይሉሃል እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ፈቃዱም ምግባርና ሃይማኖት ነው።
፳፯፤እግዚአብሔርን መፍራት አትዘንጋ።

፳፰፤እየተጠራጠርህ እግዚአብሔርን ሁለት ልብ ሆነህ አታገልግለው።

፳፱፤በሰው አፍ አትነስ ከንፈሮችህም ክፉ ነገር ከመናገር ጠብቅ።

፴፤እንዳትጎሰቁል ሰውነትህም በመከራ እንዳትወድቅ ራስህን አታኲራ። እግዚአብሔርም ሠውረህ የሠራኸው ኃጢአትህን ይገልጥብሃል።እግዚአብሔርን በመፍራት አልመጣህምና በብዙ ሰዎች መካከል በመከራ ይጥልሃል።በልብህም ክዳት አለ።