Saturday, October 5, 2013

ምዕራፍ ፪

                       ለእግዚያብሔር ታማኝ ስለ መሆን


፩፤ ልጄ ለእግዚአብሔር ትገዛ ዘንድ ወደ ገዳም ብትሄድ ሰውነትህን ለመከራ አዘጋጅ።

፪፤ ልብህን በምግባር አቅና መከራውንም ታገሥ አትጠራጠር ፤በመከራውም ብትጨነቅ አትጠራጠር።
 
፫፤ ነገር ግን እግዚአብሔርን ተከተለው ኋላ በፍጻሜ ዘመንህ ክብርህ ትበዛ ዘንድ አትተወው።

፬፤፭፤ የደረሰብህን መከራ ሁሉ በትዕግስት ተቀበል።ወርቅን በእሳት እንዲፈትኑት ጻድቅንም ሰው ችግር በሚያመጣ መከራ ይፈትኑታልና ገንዘብ በተቸገርክበት ወራት መከራውን ታገሥ።
 
፮፤ እግዚአብሔርን እመነው እንጂ ይረዳሃል ፤ሥራህን አቅና በሱም እመን።
 
፯፤ እግዚአብሔርን የምትፈሩት ሰዎች ቸርነቱን ደጅ ጥኗት በመከራ እንዳትወድቁ ከሱ አትራቅ።
 
፰፤ እግዚአብሔርን የምትፈሩት ሰዎች እመኑት ዋጋችችሁንም እንዳታጡ ሁኑ።
 
፱፤ እግዚአብሔርን የምትፈሩት ሰዎች በጎ ረድኤቱን ተስፋ አድርጓት ዘለዓለም ጸንቶ የሚኖር ደስ የሚያሰኝ ቸርነቱን ተስፋ አድርጉ።
 
፲፤ በዘመን የቀደሙ ሰዎችን አስተውሎ በእግዚአብሔር አምኖ ያፈረ ማነው።እወቁ እሱን በመፍራት መከራውን የታገሰ በመከራ እንደ ጣለው የቀረ ማነውለምኖትስ ቸል ያለው ማነው።

፲፩፤ እግዚአብሔር ይውር ባይ ነውና ርኁሩኅ ነውና ኃጢአትን ይቅርይላል ከመከራውም ቀን ያድናል።
 
፲፪፤ ለሚጠራጠር ልቡና ወዮለት ለክፉዎች ሰዎች ወዮላቸው ሥራው ሁለት ለሆነ ኃጢአቱን አብዝቶ ለሚሰራ ለኃጢአተኛ ሰው ወዮለት።

፲፫፤ ለሚጠራጠር ሰው ወዮለት አላመነምና፤ ስለዚህ ነገር ከመከራው አያመልጥም።
 
፲፬፤ ዋጋቸውን ላጡ ሰዎች ወዮላቸው እግዚአብሔር በመዓቱ በተመላባቸው ጊዜ ምን ያደርጉ ይሆን።
 
፲፭፤ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሰዎች ቃሉን አይረሱም የሚወዱትም ሰዎች አምልኮቱን ዘጠኙን ሕግጋት ይጠብቃሉ።
 
፲፮፤ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሰዎች ፈቃዱን ይፈጽማሉ የሚወዱትም ሰዎች ሕጉን ይጠበቃሉ።
 
፲፯፤ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሰዎች ልቡናቸውን ለመከራ ያዘጋጃሉ።ሰውነታቸውንም መከራውን ያስቧታል ቸርነቱ እንደ ገናንነቱ ብዛት መጠን ነውና።
 
፲፰፤ በሰው እጅ ከመውደቅ በእግዚአብሔር እጅ መውደቅ ይሻላልና ብለው ሰውነታቸውን በፊቱ መከራውን ያስችሏታል።