Saturday, October 5, 2013

ምዕራፍ ፲፯




፩፤ እግዚአብሔር፥ አዳምን ከምድር ፈጠረው፤ ዳግመኛም ወደ ምድር ይመልሰዋል።

፪፤ ዘመንን፣ ቀንን፣ በቊጥር ሰጣቸው፤ በውስጧም ያለውን ፍጥረት ሁሉ አስገዛቸው።

፫፤ እየራሳቸው ኃይልን አሳደረባቸው፤ በምሳሌውም ፈጠራቸው።

፬፤ ፍጥረቱ ሁሉ፦ ይፈሩዋቸው ዘንድ፥ እንዲፈሩዋቸው አደረገ።

፭፤ ከብቶችንና አውሬዎችን፣ ወፎችንም፤ ይገዟቸው ዘንድ እንዲገዟቸው አደረገ።

፮፤ አንደበትንና ቃልን፣ ዦሮንንና ዓይንን፣ በሚያስቡ ገንዘብ ልቦናንም ሰጣቸው። 

፯፤ ጥበብን፥ ማወቅንም አጠገባቸው፤ ክፉንና በጎንም አሳያቸው።

፰፤ የሥራውን ገናንነት፥ መፈራቱንም ያሳያቸው ዘንድ፤ በልቦናቸው ፍርሃትን አሳደረባቸው።

፱፤ የከበረ ስሙን ያመሰግኑት ዘንድ።

፲፤ የሥራውንም ገናንነት፥ ይናገሩ ዘንድ፤ ፍርሃትን አሳደረባቸው።
  
፲፩፤ ጥበብን ሰጣቸው፥ የሚያድናቸው ሕጉንም አወረሳቸው።

፲፪፤ ለዘለዓለም ጸንቶ የሚኖር፥ መሐላንም ተማማላቸው፤ ፍርዱንም ነገራቸው። 

፲፫፤ የጌትነቱንም ገናንነት ዓይኖቻቸው አዩ። 

፲፬፤ ከኃጢአቱ ሁሉ፥ ተጠበቁ አላቸው።

፲፭፤ የጌትነቱንም ቃል፥ ዦሮቻቸው ሰሙ፤ ሁሉንም፥ ባልንጀራችሁን ውደዱ ብሎ አዘዛቸው።

፲፮፤ ሥራቸውም፥ ሁለጊዜ በፊቱ ነው፤ ካይኖቹም የሚሠወሩበት የላቸውም።

፲፯፤ ለአሕዛብ ሁሉ፥ ነገሥታቱን አነገሠላቸው።

፲፰፤ እስራኤል ግን፥ የእግዚአብሔር እድል ሆነ።

፲፱፤ ሥራቸውም ሁሉ፥ በፊቱ እንደ ፀሐይ ነው፤ ዓይኖቹም፥ ሁለጊዜ ሥራቸውን ያያሉ። 

፳፤ ኃጢአታቸውም፥ ከሱ አልተሠወረችም፤ በደላቸውም ሁሉ፥ በእግዚአብሔር ፊት የተገለጠ ነው።

፳፩፤ የሰው ምጽዋቱ፥ ከሱ ጋራ እንደ ማኅተም ነው። 

፳፪፤ የሰው ዋጋው፥ እንደ ዓይን ብለኔ ትጠበቅለታለች። 

፳፫፤ ኋላ ተመልሶ፥ ዋጋቸውን ይሰጣቸዋል፤ የኃጢአታቸውንም ፍዳ፥ ወደ ራሳቸው ይመለሳል። 

፳፬፤ ነገር ግን፥ ንስሐ የሚገቡትን ምክንያት ሰጣቸው፤ ተስፋቸውን ያጡ ሰዎችንም፥ ደስ አሰኛቸው። 

                                የንሰሐ ጥሪ                
 
፳፭፤ በንስሐ፥ ወደ እግዚአብሔር ተመለስ፤ ኃጢአትንም ተዋት፥ ከኃጢአትህ ተመልሰህ፣ በፊቱ ተለማመጥ።

፳፮፤ ፈጽመህ ከኃጢአትህ፥ በንስሐ፣ ወደ እግዚአብሔር ተመለስ፤ ኃጢአትን ሁሉ ጥላ፥ የእግዚአብሔርንም ፈቃድ ፈጽም።

፳፯፤ በሕይወት ሳሉ፥ እንደሚገዙለት ሰዎች፤ እግዚአብሔርን፥ በመቃብር የሚያመሰግነው ማነው።

፳፰፤ የሞተ ሰውን ግን፥ ንስሐ እንደ ኢምንት አለፈው፤ በሕይወት ሳለህ፥ ደስ እያለህ፤ እግዚአብሔርን አመስግነው።

፳፱፤ የእግዚአብሔር፥ ቸርነቱ ብዙ ነው ነውና የሚገዙለትን ሰዎች ይቅር ይላቸዋል። 

፴፤ ሰው፥ ሟች ስለ ሆነ፤ ሰው ሁሉ፥ በሕይወት ጸንቶ መኖርን አይችልምና ይቅር ይላቸዋል።

፴፩፤ ከፀሐይ፥ የሚነጻ ምን አለ፤ እሱስ ስንኳ ያልፋል። እንዲህ መሆን ሳለ፥ ደማዊና ሥጋዊ፤ ክፉ ነገርን ያስባል። 

፴፪፤ እሱ ግን፥ የሰማይን ምጥቀት ያውቃል፤ ሰው ሁሉ ግን፥ አመድ፣ ትቢያ፤ ነው።