Saturday, October 5, 2013

ምዕራፍ ፲፰




1 ለዘለዓለም ሕያው የሆነ እርሱ ሁሉን በአንድነት ፈጠረ፡፡ 

2 አውነተኛ እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ 

3 ሥራውን ያውቅ ዘንድ ማንንም አላሰናበተውም፤ የገናናነቱንስ ፍለጋ ማን መርምሮ ያውቃል?

4 ከሀሊነቱንስ ማን መርምሮ ያውቃል? ቸርነቱንስ ማን ጠንቅቆ ይናገራል?
 
5 መጨመርም የለም መቀነስም የለም፤ የእግዚአብሔርን የጌትነቱን ፍለጋ የሚያገኝ የለም፡፡ 

6 ሰውን በፈጠረው ጊዜ ያን ጊዜ ያዝዘዋል፤ ዘመኑንም ባስጨረሰው ጊዜ ያን ጊዜ ያሳርፈዋል፡፡ 

7 ሰው ምንድን ነው? ጥቅሙስ ምንድን ነው? 

8 በጎነቱ ምንድን ነው? ክፋቱስ ምንድን ነው? የዘመኑ ቁጥር ቢበዛ መቶ ዓመት ነው፤ 

9 በባሕር ውስጥ እንደ አንዲት የውኃ ጠብታ፣ ከአሸዋውም ሁሉ እንደ አንዲት የአሸዋ ቅንጣት፣ እንዲሁ በዘለዓለማዊነት ዓመታት ዘንድ ዘመኑ ጥቂት ነው፡፡

10 ስለዚህ ነገር እግዚአብሔር ይታገሣቸዋል፡፡ ምሕረቱን አሳደረባቸው፡፡ 

11 ፍጻሜያቸው ክፉ እንደ ሆነ አይቶ ዐወቃቸው፤ ምሕረትን እንዲሁ አብዝትዋልና፡፡ 

12 ሰው ባልንጀራውን ብቻ ይቅር ይላል፣ እግዚአብሔር ግን ፍጥረቱን ሁሉ ይቅር ይላል፤ 

13 ይቆጣል፣ ይገርፋል፣ይቅር ይላል፣ እረኛም መንጋውን እንዲመልስ ይመልሳል፡፡ በተግሣጽ የሚታገሡትን ሕጉንም የሚከተሉትን ሰዎች ይቅር ይላቸዋል፡፡

                                 የተወደደ ምጽዋት

14 ልጄ ሆይ በደስታ መካከል ኀዘንን አታስገባ፣ በምትሰጠውም ሁሉ ክፉ ነገርን አትናገር፡፡ 

15 ዝናም ዋዕይን የሚያቀዘቅዘው አይደለምን? እንዲሁ በጎ ቃል ከመስጠት ይሻላል

16 እነሆ እንግዲህ ከመስጠት መልካም ቃል አይሻልምን ? ሁለቱም ሁሉ በጻድቅ ሰው ዘንድ ይገኛሉ፡፡

17 ንፉግ ልቡናውን ደስ ሳይለው ይሰጣል፡፡ ሰነፍም ይላገዳል አያመሰግንምም፡፡

18 ሳትናገር ተረዳ፣ ሳትታመምም ዳን፡፡ 
 
19 ሳይፈርድብህ ራስህን መርምር፤ በመከራህም ጊዜ ይቅርታን ታገኛለህ፡፡ 

20 ሳትደክም ራስህን አዋርድ፣በበደልህም ጊዜ ንስሐ ግባ፡፡

21 ስእለትህን ፈጥነህ ስጥ ሳትሞትም ጽድቅን ሥራት፡፡ 

22 ሳትሳለም አስቀድመህ ስእለትህን አዘጋጅ፤ እግዚአብሔርን እንደሚፈታተነው ሰው አትሁን፡፡ 
 
23 በተቆጣህም ጊዜ የሞትን ቀን ዐስብ፤ የፍርድህንም ቀን ዐስብ፤ ንስሓም ግባ ጸልይም፡፡ 

24 በጥጋብህ ወራት የረኀብህን ወራት ዐስብ፡፡ በተድላህም ወራት የችግርሀን ወራት ዐስብ፡፡

25 ኑሮ ከጧት እስከ ማታ ድረስ ትለዋወጣለችና፡፡ ሁሉም በእግዚአብሔር ዘንድ አንድ ጊዜ ፈጥኖ ይደረጋልና፡፡ 
 
26 ብልህ ሰው ግን ፈርቶ በሁሉ ይጠበቃል፤ 

27 አስተዋይ ሰው ሁሉ ጥበብን ያገኛታል፤ ያገኛትንም ሰው ታስመሰግነዋለች፣ ተስከብረዋለች፣ 

28 ነገር ዐዋቂዎች ራሳቸው በልቡናቸው ይራቀቃሉ፤ የተረዳ ምሳሌንም ይናገራል፡፡

29 አትሂድ፣ የኀጢአትንም ፈቃድ አትከተል፤ከክፉ ፍትወት ራቅ፡፡ 

30 ለሰውነትህ የምትወድደውን ከሰጠኻት ጠላትህን በአንተ የጨከነ ታደርገዋለች፡፡ 

31 በተድላ ብዛት ደስ አይበልህ፤ከእርሱም ጋር ደስ ይልህ ዘንድ አትለምን፡፡ 

32 እንዳትያዝ አንተ ደሃ ሳለህ በከረጢትህም ምንም ሳይኖርህ አትበደር፡፡