፩. ጠፈርን በህዋው ላይ አጸናት ሰማይንም ማየት በጸሐይ ብርሃን ነው፡፡
፪. ብርሃኑን ያሳይ ዘንድ ጸሐይን ያወጣል የሰማይ ብርሃን ሥራትም ድንቅ ነው፡፡
፫. በዋዕዩም አገሩን ያቃጥላል ዋዕዩንስ ማን ይቀዋወመዋል፡፡
፬. ዋዕዩም እንደሚነድ እሳት ያቃጥላል የጸሐይ ሦስተኛ ብርሃኗ ተራሮችን ያቃጥላቸዋል፡፡ የእሳት ዋዕይ ከሱ ይገኛል ብርሃኑንም ማየት አይን ያጣምማል፡፡
፭. የፈጠረው እግዚአብሔርንም ደግ ነው በቃ ሁሉም ፈጥኖ ይሄዳል፡፡
፮. ጨረቃም ለሰው ሁሉ ምልክት ነው ላገሩም ሁሉ ምልክት ነው በሷም ቀን ይለያል፡፡
፯. በጨረቃም የበዓላቱ ምልክት ይታወቃል ሕጸጽ እያደረገ የሚያልቅ ብርሃን እሱ ነው፡፡
፰. ጨረቃስ እንደስሟ ናት ከከዋክብትም እንድትበልጥ ድንቅ ነው በሰማ ሰራዊት በከዋከብት ሥራትም ሕጸጽና ምላትን እንድታፈራርቅ ድንቅ ነው በሰማይ ሰራዊት በከዋክብትም መካከል ሁና ታበራለች፡፡
፱. የሰማይ ጌጥ የከዋክብት ብርሃን ነው፡፡ እግዚአብሔር በፈጠረው በጠፈር ሁነው ለዚህ ዓለም ያበራሉ፡፡
፲. በጌትነቱ ቃል ጸንተው ይኖራሉ ከሥራታቸውም ወጥተው አያልፉም፡፡
፲፩. ብርሃኑ ፈጽሞ ያማረ ነውና ቀስተ ደመናወን አይተህ ፈጣሪውን አመስግነው፡፡
፲፪. በሰማይ ይከፈላል ብርሃኑም ይከበዋል የእግዚአብሔርም ቃሉ ይከፍለዋል፡፡
፲፫. በትዛዙም በረድ ይዘንባል መብረቅም በፈቃዱ ፈጥኖ ይወርዳል፡፡
፲፬. ስለዚህ ነገር እግዚአብሔር ቦታውን ይገልጣል ደመናትም እንደ ወፎች ይበራሉ፡፡
፲፭. በገናንነቱም ደመናትን ያጸናቸዋል የበረድ ድነጋይም ይከፈላል፡፡
፲፮. በጎበኛቸውም ጊዜ ተራሮች ይነዋወጣሉ በፈቃዱም የምሥራቅ ነፋስ ይነፍሳል፡፡
፲፯. የመብረቁም ቃል ምድርን ያስፈራታል የምዕራብ ነፋስም ሰውነትን ያደርቃታል ጉምንም እነደሚበሩ ወፎች ይበትነዋል አወራረዱም እንደ አንበጣ አወራረድ ነው፡፡
፲፰. ያነጣጡም መልክ ለዓይን ድንቅ ነው በረድን እነደ ጨው ይቀላቅላታልና ዝናምነቱም ለልብ ድንቅ ነው፡፡
፲፱. ጉምንም በዚህ ዓለም ይበትነዋል ውርጭም ከረጋ በኋላ ሽፎ እንደሆነ እንደ ብርሌ ስባሪ ብልጭ ይላል፡፡
፳. የቀዘቀዘ የምሥራቅ ነፋስም ይነፍሳል ውርጭም በውኃ ላይ ይረጋል በውኃው አዟሪ ላይ ይቆማል እንደ ብረት ልብስም በውኃ ላይ ጸንቶ ይኖራል ውኃይቱንም ይሸፍናታል፡፡
፳፩. ተራራውን ይበላል ምድረ በዳውንም ያቃጥላል ሥሩንም እነደ እሳት ያደርቀዋል፡፡
፳፪. የሰው ሁሉ ሕይወቱ ዝናም ፈጥኖ ቢዘንም ዝናምም ወደ ምድር በወረደ ጊዜ ደስ ያሰኛል፡፡
፳፫. በእግዚአብሔር ምክር ውኃው ይደርቃል ከዚህ በኋላ ኢያሱ ጸሐይን አቆመ፡፡
፳፬. በባሕርም የሚሄዱ ሰዎች መከራዋን ይናገራሉ እኛም ሰምተን እናደንቃለን፡፡
፳፭. በዚያም ሥራው ፈጽሞ ድንቅ ነው፡፡ ከብትን መግዛት በየወገኑ ነው፡፡
፳፮. በጎ መዓዛ አድርጎ ሊቀበለው ከነሳቸውም መሥዋዕት ይሠዋለታል በቃሉም ሁሉ ይደረጋል፡፡
፳፯. ብዙ ነገርን እንናገራለን የነገሩ መጨረሻ እሱ ብቻ ነው እንጂ ነገር ግን መጨረስ አንችልም፡፡
፳፰. ከፍጥረት ሁሉ እሱ ይበልጣልና እሱን ማመስገን ምን ያህል እንችላለን፡፡
፳፱. እግዚአብሔር ልውጥ ነው የሚያስፈራ ነው ልቁንም ገናንነቱም ያስፈራል ሓይሉም ድንቅ ነው፡፡
፴. ጨርሳችሁ ማመስገንን አትጠነቀቁምና ምንም ባትጠነቀቁ የተቻላችሁን ያህል እግዚአብሔርን አመስግኑት አግኑት፡፡ ዳግመኛም ከዚህ ሁሉ በልጣል በፍጹምእውቀታችሁም አግኑት አትደርሱበትምና ምንም ባትደርሱበት እሱን ማመ ስገንን ቸል አትበሉ፡፡
፴፩. ከቶ የሚነግረን ማነው በገናንነቱስ ልክ ማን ያገነዋል፡፡
፴፪. ማይታየው ከዚህ የሚበልጠው ፍጥረቱ ብዙ ነው ያየነው ፍጥረቱ ግን ጥቂት ብቻ ነው፡፡
፴፫. እግዚአብሔር ሁሉን ፈጥሯልና ለደጋጎች ሰዎች ጥበብን ሰጣቸው፡፡