Sunday, October 6, 2013

ምዕራፍ ፳፱



ስለ ማበደርና መበደር

፩፤ምጽዋትን የሚመጸውት ሰው ለእግዚአብሔር በማደሩ ነው በእጁም የሚበቃ ገንዘብ ያለው ፈቃዱን ያደርጋል፡፡ 

፪፡በተድላው በደስታው ጊዜ ከሱ ጋር ደስ ይልህ ዘንድ በተቸገረ ጊዜ ለባልንጀራህ አበድረው፡፡

፫፤ወዳጅህን ጠብቅ ከእሱም ጋር ተማመን በወደድሃትም ጊዜ ጽድቅን ታገኛታለህ 

፬፡ የብድርን ገንዘብ በመሬት ላይ ወድቆ ያገኙ የሚመስላቸው ሰዎች ብዙ ናቸው ያበደሩዋቸውን በመከራቸውም ጊዜ የረዷቸውን ባለጸጎች አደከሟቸው፡፡ 

፭፤ እስኪበደርህም ድረስ እራስ ህን ይስምሃል ቃሉንም ያደክማል ገንዘብንም እስኪወስድ ድረስ ያባብልሃል በተከፈልከው ጊዜ ግን ቀጠሮህን ያረዝምብሃል በገንዘብህም ጠብና ክርክርን ይከፍልሃል፡ ያደክምሃል ቀጠሮህንም ያራዝማል፡፡

፮፤ እኩሌታውንም ቢከፍልህ በጭንቅ ነው ዳግመኛም እሱን በምድር ላይ ወድቆ ያገኘኸው ይመስልሃል ይህስ ካልሆነ ገንዘብህን ሁሉ ታጣለህ ዳግመኛም ጠላት ይሆንሃል ስድቡን ይሰድብሃል እርግማንም ይረግምሃል ሲያከብርህም ያዋርድሃል

፯፤ገንዘባቸውን እንዳያጡ ከሰውም እንዳይጣሉ በመፍራትና ጠብን ባለመውደድ ገንዘባቸውን የማያበድሩ ሰዎች ብዙ ናቸው፡፡

            ስለ ምጽዋት

፰፤ድሃውን ግን ታገሰው ምጽዋቱንም ስጠው አልፈኸው አትሂድ፡፡ 

፱፤የምጽዋትን ነገር የሚናገር አንቀጽ ይህ ነው ችጋረኛ ነውና ድሃውን በምጽዋት ተቀበለው ባዶውንም አትመልሰው፡፡ 

፲፤ባልንጀራህንና ወዳጅህን ክታጣ ወርቅህ ተቀብሮ ኪዝግ በድንጋይም ሥር ተቀብሮ ቢጠፋ፡፡

፲፩፤እግዚአብሔር መጽውት ብሎ ስላዘዘህ ወርቅህን ከተቀበረበት አውጥተህ መጽውት ከወርቅ ድልብ ይልቅ ፈጽሞ ምጽዋት ይጠቅምሃል፡፡

፲፪፤ ምጽዋትን በድሆች ቤት አድልባት እሷ ትሻላለች ከመከራህም ሁሉ አንተን ማዳን ትችላለች፡፡ 

             ስለ ዋስትና

፲፫፤ በጦር ቢሆን በመሳሪያም ቢሆን እሷ ቀድማ ጥንተ ጠላት ህን ድል ትነሳልሃለች የለት ጠላት ህንም ታጠፋልሃለች፡፡ 

፲፬፤ ደግ ሰው ወዳጁን ይዋሰዋል የማያፍር ሰው ግን ባልንጀራውን ቸል ይላል፡፡

፲፭፤ ስላንተ ፋንታ ሰውነቱን አሳልፎ ሰጥቷልና የተዋሰህን ሰው ዋጋውን አትንካበት፡፡

፲፮፤ ጠብን ለማጥፋት መዋስ ደግ ነገር ነው፡፡

፲፯፤ኃጢአተኛ ሰው ግን ያዳነውን ሰው ዋጋ ይዘነጋል፡፡ 

፲፰፤ መዋስ ብዙ ሰዎችን አሳዘነ እንደ ማዕበልም አወካቸው አርበኞች ሰዎችንም አሳታቸው ልዩ ወደሆኖ አህዛብም አገር እንዲሰደዱ አደረጋቸው፡፡ 

፲፱፤ ኃጢአተኛ ሰው በመዋስ ይጠፋል ለትርፍም የሚሳሳ ሰው በመከራ ይወድቃል፡፡ 

፳፤የተቻለህን ያህል ባልንጀራህን ተቀበል ነገር ግን እንዳያስትህ እራስ ህን ጠብቅ 

፳፩፤ የኑሮህ መጀመሪያ የምትበላው እህል የምትጠጣው ውሃ የምትለብሰው ልብስ ነው ቤትህን ግን እፍረ ህን የምት ሰውርበት ነው፡፡

፳፪፤ በሌላ ሰው ገንዘብ ለባእድ ቤት ስት ዘጋጅ ደስ ሲልህ በቤትህ ምሰሶ ስር ብትቸገር ይሻልሃል፡፡

፳፫፤ለታናሹም ለታላቁም በጎ ስራን ሥራ በጎ ነገርንም ተናገር፡፡ 

፳፬፤ ለመቀላወጥ ካንዱ ቤት ወዳንዱ ቤት የሚሄድ ሰው አነዋወሩ ክፉ ነው ባደርህበትም ቦታ ክፉ ነገር እንዳትናገር እወቅ፡፡

፳፭፤ ይኸስ ካልሆነ ትበላለህ ትጠጣለህ ምስጋና የለህም ከዚህ ሁሉ ጋራ ክፉ ነገር ይመልሱልሃል፡፡

፳፮፤ በገንዘብ በተዘጋጀ ህ ጊዜ ግን አማቻችን ገብተህ ማዕድን ሥራ ያለህንም አብላን ይሉሃል።

፳፯፤ ብትቸገር ግን ቤተሰባችን ውጣ አማቻችን ደረሰ ቤታችንን እንወዳለን ይሉሃል፡፡

፳፰፤ ይህ ነገር ባዋቂ ሰው ዘንድ ጭንቅ ነው ያሳደርከው ሰው ያዋርድሃል ያበደርከውም ሰው ይሰድብሃል፡