Saturday, October 5, 2013

ምዕራፍ ፲፭




፩፤ እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው እንዲህ ያደርጋል፥ ሕጉንም የሚጠብቅ ሰው ያገኛታል። 

፪፤ እንደናቱ ትከባከበዋለች፥ እንደ ቆንጆ ሴትም ትዋሐደዋለች። 

፫፤ የጥበብን እህል ትመግበዋለች፥ የእውቀትንም ውኃ ታጠጣዋለች።

፬፤ የሚጠብቃትም ሰው በመከራ አይወድቅም፥ የሚታመንባትም ሰው አያፍርም።

፭፤ ከባልንጀራው ይልቅ ታገነዋለች፥ በብዙ ሰዎች መካከልም ነገር ይናገራል። 

፮፤ ተድላ ደስታ ትሰጠዋለች፥ ተድላ ደስታ ያለበት ዘውድንም ታቀዳጀዋለች፣ ስሙንም ለዘለዓለሙ ያስጠራል።

፯፤ ሰነፎች ግን አያገኟትም፥ ኃጢአተኞች ሰዎችም አያይዋትም።

፰፤ ከትዕቢተኞችም ሰዎች የራቀች ናት፥ አሰተኞችም አያስቧትም።

፱፤ እግዚአብሔርን በመፍራት የሚናገር አይደለምና ኃጢአተኛ ሰው ባንደበቱ የተናገረው ነገር ያማረ አይደለም። 

፲፤ ምሳሌን በጥበብ ይናገራታል፥ እግዚአብሔርም የሚማራትን ሰው ይረዳዋል። 

፲፩፤ ስለ እግዚአብሔር ብዬ ከሥጋ፣ ከጠጅ ተከለከልሁ አትበል፤ እሱ የጠላውንም አትሥራ።

፲፪፤ ኃጢአት ሠርተህ እሱ አሳተኝ አትበል፥ እግዚአብሔር የረከሰውን ሰው ሁሉ ጠልቷልና፤ እሱስ ኃጢአተኛ ሰውን አይወድም።

፲፫፤ የሚፈሩትንም ሰዎች ይወዳቸዋል። 

፲፬፤ እሱ ቀድሞ ሰውን፥ በንጽሐ ጠባይዕ ፈጥሮ፤ በወደደው ሥራው ተወው። 

፲፭፤ ትእዛዙን ትጠብቅ ዘንድ፥ ሃይማኖቱንም ታጸና ዘንድ ብትወድ ግን ፈቃዱ ነው። 

፲፮፤ እጅህን በመረጥኸው ትጨምር ዘንድ እነሆ፦ እሳትና ውኃን አኖረልህ። (ጽድቅና ኃጢአትን) 

፲፯፤ ሞትና ሕይወትም በሰው ፊት ነው፥ ከነሳቸው የመረጠውን ሥላሴ ይሰጡታል። 

፲፰፤ የእግዚአብሔር ጥበቡ ብዙ ነውና ዕውቀቱም የጸና ነውና ሁሉን ያውቃል፤ ሁሉን ያያል።

፲፱፤ ዓይኖቹም፥ የሚፈሩትን ሰዎች ይመለከታሉ፤ እሱም የሰውን ሥራ ሁሉ ያውቃል።

፳፤ ኃጢአት ይሠራ ዘንድ እሱስ ያዘዘው የለም፥ ይበድልም ዘንድ ማንም ማን አላሰናበተውም።