Saturday, October 5, 2013

ምዕራፍ ፲




፩ ጠቢብ ንጉሥ ሕዝቡን ይመክራል፥ አስተዋይ ዳኛም ሥርዐትን ይሠራል፡፡ 

፪ ሎሌውም እንደ ሕዝቡ አለቃ ነው፤ የከተማው ገዥ እንደሚሠራው በውስጧ የሚኖሩ ሰዎች ይሠራሉ፡፡

፫ አላዋቂ ንጉሥ ሕዝቡን ያጠፋል፤ ሀገርም በሽማግሌዎች ጥበብ ትጸናለች፡፡

፬ የምድር ግዛት በእግዚአብሔር እጅ ነው፥በጊዜውም የሚጠቅመውን ሰው በእርስዋ ላይ ያስነሣል፡፡

፭ የሰው በረከቱ በእግዚአብሔር እጅ ነው፥ በጸሓፊም ሰውነት ክብሩን ያኖራል፡፡

                         በትዕቢት የሚመጣ ኅጢአት

፮ ባልንጀራህን በሳተበት ሁሉ አትንቀፈው፥ በነቀፋህም ምንም ክፉ ነገር የምታደርግበት አይኑር፡፡

፯ ትዕቢት በእግዚአብሔርና በሰው ዘንድ የተጠላ ነው፥ከሁሉም ዐመፅ ትከፋለች፡፡

፰ መንግሥትም ስለ ዐመፅና ክርክር፥ ስለ ገንዘብም፥ካንዱ ወገን ወደ ሌላ ወገን ትፈልሳለች፡፡

፱ እንግዲህ ትቢያና ዐመድ የሚሆን፥ በሕይወትም ሳለ ሰውነቱ የሚተላ ሰው ለምን ይታበያል?

፲ የሰው ቊስልን ባለ መድኀኒት ያድነዋል፤ንጉሥ መባል ግን ለዛሬ ብቻ ነው፥ነገም ይሞታል፡፡

፲፩ ሰውም ከሞተ በኋላ የትል ዕድል ፋንታ ይሆናል፡፡

፲፪ የትዕቢት መጀመርያ ሰውን ከእግዚአብሔር ትለየዋለች፤ልቡናውንም ከፈጣሪ ታርቀዋለች፡፡

፲፫ ትዕቢት የኀጢአት መጀመርያ ናት፤ በአጸናትም ሰው ላይ ርኵሰትን ታበዛበታለች፥ ስለዚህም እግዚአብሔር የትዕቢተኞችን ፍዳ ይገልጣል፥ፈጽሞም ያጠፋቸዋል፡፡

፲፬ እግዚአብሔር ያለቆችን ዙፋን ያፈርሳል፤ በእነርሱም ፋንታ የዋሃንን ይሾማል፡፡

፲፭ እግዚአብሔር የአሕዛብን ሥራቸውን ነቀለ፥በእነርሱም ፋንታ ትሑታንን ተከለ፡፡

፲፮ እግዚአብሔር የአሕዛብን ሀገሮች አጠፋ፥ እስከ ምድር መሠረት ድረስ አጠፋቸው፡፡

፲፯ ፈጽሞም አጠፋቸው፥ስም አጠራራቸውንም ከምድር ደመሰሰ፡፡

፲፰ ትዕቢት ለሰው የተፈጠረ አይደለም፥ ቊጣና ጥፋትም ከሴት ለሚወለድ ሰው አይደለም፡፡

                  ክብር ስለሚገባቸውና ስለማይገባቸው

፲፱ የሰው ዘር የከበረ ነው፥ የከበረ ዘር ማንነው? እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሰዎች አይደሉምን? 

፳ የሰው ዘር የጐሰቈለ ዘር ነው፥ ጐስቋላ ዘር ማንነው? የእግዚአብሔርን ትእዛዝ የማይጠብቁ ሰዎች ዘር አይደለምን? 

፳፩ ዳኛ ከባልንጀራው ይልቅ የከበረ ነው፥ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሰዎች ግን ከእርሱ ይልቅ ይከብራሉ፡፡

፳፪ ለባለጸጋውና ለከበርቴው ለድሃውም ክብራቸው እግዚአብሔርን መፍራት ነው፡፡

፳፫ ድሃውን ስለ ድህነቱ ይንቁት ዘንድ አይገባም፥ኀጢአተኛውንም ሰው ስለ ባለጸግነቱ ያከብሩት ዘንድ አይገባም፡፡

፳፬ ታላላቆችና አለቆች፥ መኳንንቱም ይከብራሉ፤
 ከእነርሱም እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰውን የሚበልጠው የለም፡፡

፳፭ ጠቢብ ቤተ ሰብ በንጹሕ ያገለግላል፥ ዐዋቂ ሰውም አይነቅፈውም፡፡

፳፮ ሥራህን ስትሠራ አትራቀቅ፥ በችግርህም ወራት አትመካ፡፡

፳፯ ከሚዞርና ከሚመካ፥ ምግቡንም ከማያገኝ ሰው ይልቅ፥ የሚያርስና የሚቈፍር ይሻላል፡፡

፳፰ ልጄ ሆይ፥ በየዋህነትህ ሰውነትህን ደስ አሰኛት፥የተቻለህንም ያህል አዘጋጃት፡፡

፳፱ ለራሱ የሚነፍግ ለማን ቸር ይሆናል? ሰውነቱን የማያዘጋጃትን ሰውስ ማን ያመሰግነዋል? 

፴ ድሃውን ስለ ጥበቡ ያመሰግኑታል፥ ባለጠጋውን ግን ስለ ባለጠግነቱ ያመሰግኑታል፡፡

፴፩ በተቸገረ ጊዜ የማያዝን ሰው፥ በተዘጋጀ ጊዜ እንዴት ደስ ይለው?